ጅግጅጋ(cakaaranews)እሁድ፤ሐምሌ 15/2010 ዓ.ም በኩዬት የኢትዮጵያ ሶማሌ ክልል ተወላጅ ዲያስፖራ ኮሙኒቲሊቀመንበር በጅግጅጋ ገራድ ዊልዋል ዓለምአቀፍ ኤርፖርት ሲደርሱ አቀባበል እንደተደረገላቸው ተገለፀ። በአቀባበል ሥነ-ስርዓቱ ላይ የክልሉ ዲያስፖራ ቢሮ ሃላፊን ጨምሮ ሌሎች የክልሉ ከፍተኛ የሥራ ሃላፊዎች ደማቅ አቀባበል አደርጎላቹዋል።
ከበርካታ ዓመታት የውጭ ሃገር ቆይታ በኋላ በኩዬት ሃገር የሚኖሩ የኢትዮጵያ ሶማሌ ክልል ተወላጆች ሊቀመንበር አቶ መሀመድ ዚያድ አብዱራህማን ጅግጀጋ ከተማ መግባታቸው ተገለፀ። በአቀባበል ሥነ-ስርዓቱ ላይ በክልሉ የዲያስፖራ ማስተባበሪያ ቢሮ ሃላፊና በክልሉ ፕሬዝዳንቱ የቅሬታ አፈታት አማካሪ አቶ አብዱረዛቅ ሰሀኔ፣ የክልሉ ውሃ ሃብት ቢሮ ሃላፊ አቶ አህመድ አብዲ፤ሌሎች የክልሉ ከፍተኛ የሥራ ሃላፊዎችና የክልሉ ሄጎ የወጣቶች ንቅናቄ አባላት ለሊቀመንበሩ ደማቅ አቀባበል ማድረጋቸው የዲያስፖራ ማስተባበሪያ ቢሮ ሃላፊ ገለፀ።
በዚህም ”ዛሬ በዚህ በጅግጀጋ ገራድ ዊልዋል ዓለምአቀፍ ኤርፖርት የተገኘነው በኩዬት የኢትዮጵያ ሶማሌ ክልል ተወላጆች ሊቀመንበርን ለመቀበል ነው። ግለሰቡ ያለበትን ትልቅ ሃገራዊ ሃላፊነት መቶ በመቶ ሊባል በሚችል መልኩ በሃገር ውስጥም ይሁን በውጭ በሄደበት የሚወጣ ነው። በተለይ በክልሉ ልማት፣ እድገትና በመልካም አስተዳደር ግንባታው ላይ ያላሰለሰ ጥረት ከሚያደርጉት መካከል የሚመደብ ነው። በዚህ አጋጣሚ አቶአህመድ ዚያድን ለመቀበል እዚህ በመገኘቴ በራሴና በዲያስፖራ ማስተባበሪያ ፅ/ቤት ሥም የተሰማኝን ደስታ ለመግለጽ እወዳለሁ። በድጋሚም እንኳን ወደ እናት ምድርህ በሰላም መጣህ ለማለትም እፈልጋለሁ።” ሲሉ አቶ አብዱረዛቅ ሰሀኔ ገልፀዋል።
በተጨማሪም የክልሉ ውሃ ሀብት ቢሮ ሃላፊ አቶ አህመድ ”ዛሬ እዚህ የመጣነው በኩዬት የኢትዮጵያ ሶማሌ ክልል ተወላጆች ሊቀመንበር አቶ አህመድ ዚያድን ለመቀበል ነው። በሌሎች በተለያዩ ሃገራት ለሚኖሩ የክልሉ ተወላጅ ዲያስፖራዎችም በቀዳሚነት ተምሳሌት ሊሆን የሚችል ነውና በድጋሚ እንኳን ደህና መጣህ እንላለን።” ሲሉ ገልፀዋል።
አቀባበል የተደረገላቸው የኩዬት ዲያስፖራ ኮሙኒቲ ሊቀመንበር አቶ አህመድ ዚያድ በበኩላቸው “ዛሬ በውስጤ ደስ ያለኝና የተለየ ስሜት ተሰምቶኛል ምክንያቱም ከክልሉ ከፍተኛ ባለሥልጣን እስከ ወጣቶቹ ሳይቀር አቀባበል አድርገውልኛል በዚህም እጅግ አድርጌ ላመሰግናቸው እወዳለሁ። እጅግ ደስ የሚያሰኝና መልካም አቀባበል ነው በጣም አመሰግናለሁ።” ሲሉ በተደረገላቸው አቀባበል እንደተደሰቱ ገልፀዋል።
የክልሉ ሄጎ የወጣቶች ንቅናቄ ሊቀመንበር በበኩሉ በውጪ ሃገራት የሚኖሩ የክልሉ ተወላጅ ዲያስፖራዎች በክልሉ ልማትና እድገት እያደረጉ ባሉት ዘርፈ ብዙ ተሳትፎ ደስተኛ መሆናቸውን ገልጿል። በተጨማሪም “ዛሬ ከኩዬት የመጣው የክልሉ ተወላጅ ዲያስፖራዎች ሊቀመንበር አቶ አህመድ ዚያድን ተቀብለናል እንደ ክልሉ ሄጎ ወጣቶችም በጣም ደስተኞች ነን የክልሉ ተወላጅ ዲያስፖራዎች በክልሉ እያደረጉ በሚገኙት የልማት፣ እድገትና የመልካም አስተዳደር ግንባታ ሥራዎች ተሳትፎ ጋርም እኛም ከጎናቸው ነን እንኳን ደህና መጣህ እንላለን።” ሲል ተናግረዋል።